የፕሬስ መግለጫ
ነሀሴ 29 ቀን 2015 ዓ.ም
አዲስ አበባ
የኢትዮጵያ ንግድ ሥራዎች ኮርፖሬሽንበ2015 በጀት ዓመት 3,993,671 ኩንታል ምርት ለገበያ አቀረበ
ኮርፖሬሽኑ የ2015 በጀት ዓመት በሀገር ውስጥ እና በወጭ ንግድ ብር 12,584,827,585 ዋጋ ያለው 3,248,878 ኩንታል የእህል፣ የአትክልትና ፍራፍሬ እና የፍጆታ እቃዎች ምርት ለማሰራጨት አቅዶ ብር 13,953,579,322 ዋጋ ያለው 3,993,671 ኩንታል ምርት በማሰራጨት የዕቅዱን በመጠን 123 በመቶ በዋጋ ደግሞ 111 በመቶ አከናውኗል፡፡ የኮርፖሬሽኑ የሽያጭ መጠን ከ2014 በጀት ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ሽያጭ ጋር ሲነፃፀር 14 በመቶ ብልጫ አለው፡፡ ከተገኘው ጠቅላላ ሽያጭ ገቢ 82 በመቶ ከሀገር ውስጥ ሽያጭ የተገኘ ሲሆን ቀሪው 18 በመቶ ከወጭ ንግድ (ኤክስፖርት) የተገኘ ገቢ ነው፡፡
በሀገር ውስጥ ገበያ ኮርፖሬሽኑ ብር 10,795,886,282 ዋጋ ያለው 3,094,073 ኩንታል ምርት ለህብረተሰቡ ለማቅረብ አቅዶ ብር 8,713,617,305 ዋጋ ያለው 2,832,037 ኩንታል ምርት እና አገልግሎት በማሰራጨት የእቅዱን በመጠን 92 በመቶና በዋጋ 81 በመቶ አከናውኗል፡፡ አፈፃፀሙ ከ2014 በጀት ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር የ44 በመቶ ብልጫ አለው፡፡
ገበያን የማረጋጋት ተግባራት
የሃገር ውስጥ ገበያን ለማረጋጋት የምርት አቅርቦት እጥረትና በየጊዜው የዋጋ ንረት የሚታይባቸውን ምርቶች በመለየት ቅድሚያ የሚሰጣቸውን መሰረታዊ የምግብ ፍጆታ ምርቶች ማለትም ዘይት፣ ስኳር፣ ስንዴ፣ ጤፍ፣ አትክልትና ፍረፍሬ፣ የታሸጉ የፋብሪካ የምግብ ምርቶችን ለሸማቹ የህብረተሰብ ክፍል፣ ለጸጥታ ሀይል፣ ለዳቦ ማምረቻ ፋብሪካዎችና ለሌሎች ተጠቃሚዎች እያቀረበ ሲሆን ለዳቦ አገልግሎት የሚውል 1,669,686 ኩንታል ስንዴ ለሃገር መከላከያ ሰራዊት፣ ለአደጋ ሥጋት ሥራ አመራ ኮሚሽን፣ ለፌዴራል ፖሊስ፣ ለፌዴራል ማረሚያ ቤትና ለሸገር ዳቦ ማምረቻ ፋብሪካ በዚህ በጀት ዓመት እንዲቀርብ ተደርጓል፡፡
በሀገራችን ያለውን የምርት አቅርቦት እጥረት ለመሸፈን በተለይም የዓለም ምግብ ድርጅት በሃገራችን ለተረጂዎች የሚያቀርበውንና ለዱቄት ለፋብሪካዎች 242,159 ኩንታል በቆሎ፣ ለመንግሥት ሠራተኞች፣ ለማረሚያ ቤቶችና ሌሎች ሸማች የህብረተሰብ ክፍሎች 57,408 ኩንታል ጤፍ፣ 42,426 ኩንታል ፍራፍሬና አትክልት፣ 11,402,300 ሊትር የምግብ ዘይት፣ 65,170 ኩንታል ስኳር፣ 68,316 ኩንታል ልዩ ልዩ የፍጆታ ሸቀጦች በማቅረብ ገበያ ለማረጋጋት ኮርፖሬሽኑ በአስቸጋሪ ሁኔታዎች ውስጥም የበኩሉን አስተዋጽኦ በማበርከት ሀገራዊ ተልእውን ለመወጣት ጥረት በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡
ለአምራቹ ገበያ የመፍጠር ተግባራት
ኮርፖሬሽኑ ተልዕኮውን ለማሳካት ከለያቸው ቁልፍ ተግባራት አንዱ አምራቾች ላመረቱት ምርት አስተማማኝ ገበያ መፍጠር ሲሆን በዚሁ መሠረት 677,235 ኩንታል እህልና ቡና፣ 45,891 ኩንታል አትክልትና ፍራፍሬ ከምርት አቅራቢዎች ግዥ አከናውኗል፡፡ እንዲሁም 821,197 ኩንታል ምርት ከፋብሪካዎች በመግዛት የገበያ ዕድል ፈጥሯል፡፡
ሀገራዊ ትኩረት የተሰጠው የሀገር ውስጥ ስንዴ ምርት ኤክስፖርት በተመለከተም በስንዴ አምራች አካባቢዎች ከሚገኙ አምራቾች፣ የሕብረት ሥራ ማህበራት፣ ዩኔኖችና ነጋዴዎች 1,041,170 ኩንታል ስንዴ ግዥ የተፈጸመ ሲሆን ከዚህ ውስጥ እስከ በጀት ዓመቱ ማብቂያ ድረስ 624,789 ኩንታል ለዓለም ምግብ ፕሮግራም /WFP/ እና የዓለም ባንክ /WB/ ፈንድ ለሚያደርገው የምግብ ዋስትና በቀጥታ ቀርቧል፡፡
ወጪ ንግድ
በሌላ በኩል ኮርፖሬሽኑ በወጭ ንግድ 633፣ 810 ኩንታል እህል፣ ቡና እና ፍራፍሬ ወደ ውጭ በመላክ 46,057,905 የአሜሪካን ዶላር ገቢ አስገኝቷል፡፡
የኮርፖሬሽኑ የምርት ስርጭት ዋጋ ከነፃ ገበያ ዋጋ ጋር ሲነፃፀር
ኮርፖሬሽኑ ከአምራቾች የገዛውን ምርት በቀጥታ ለህብረተሰቡ በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ የአቅርቦት እጥረት ለመከላከል ከሚያደርገው ጥረት ባሻገር በበጀት ዓመቱ በሀገር ውስጥ ግብይት ለህብረተሰቡ የሸጠውን ብር 8.39 በሊዮን ዋጋ ያለው ምርት በወቅቱ በነበረው የገበያ ዋጋ ቢሸጥ ሊያወጣ ይችል የነበረው ዋጋ ብር 12.91 ቢሊዮን እንደሆነ ይገመታል፡፡ በዚህም ኮርፖሬሽኑ የሸጠው አጠቃላይ ምርት ዋጋ ከገበያው ዋጋ በብር 4.52 ቢሊዮን እንደቀነሰ ይገመታል፡፡