የኢትዮጵያ ንግድ ሥራዎች ኮርፖሬሽን አብረውት ከሚሰሩ ደንበኞችና ባለድርሻ አካላት ጋር በአገልግሎት አሰጣጥ ዙሪያ የምክክር መድረክ ሰኔ 15/ 2014 ዓ.ም በአዲስ አበባ ከተማ በኢንተር ሌግዠሪ ሆቴል አካሄደ፡፡ በመድረኩ ላይ ከኮርፖሬሽኑ ጋር በገበያ ማረጋጊያ ስራዎች በትስስር የሚሰሩ ከንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስቴር፣ ከግብርና ሚኒስቴር፣ ከአዲስ አበባ ንግድና ኢንዱስትሪ ቢሮዎች፣ ከፌዴራል ሕብረት ሥራ ኤጀንሲ፣ ከኢትዮጵያ ምርት ገበያ የተወከሉ የስራ ሃላፊዎች እንዲሁም ለኮርፖሬሽኑ ምርት እና አገልግሎት አቅራቢ የመንግስት እና የግል የንግድ ተቋማት ሸማች ህብረት ስራ ማህበራት ፣ የዱቄት ፋብሪካ ባለንብረቶች ተሳትፈዋል፡፡
በመድረኩ በቀረበው የውይይት የመነሻ ጽሁፍ በኮርፖሬሽኑ ንግድ ስራ ክፍሎች እና ኮርፖሬት ሎጅስቲክስ ዳሬክቶሬት በሚሰሩ የምርትና አገልግሎት እንቅስቃሴዎች ወቅት ያጋጠሙ ችግሮች እና በደንበኞችና መካከል ያለውን ግንኙነት ለማጠናከር የሚረዱ ሃሳቦች በኮርፖሬሽኑ የአሰራር ዘዴና አገልግሎት ማሻሻያ ዳ/ዳይሬክተር በሆኑት በአቶ ትእዛዙ ኃ/ጊዮርጊስ ቀርቧል፡፡
የመነሻ ጽሁፉን ተከትሎ ከመድረኩ ተሳታፊዎች ከኮርፖሬሽኑ የአገልግሎት አሰጣጥ ጋር በተያያዘ የተለያዩ አስተያየቶችና ጥያቄዎች ቀርበዋል፡፡
በውይይቱ ኮርፖሬሽኑ ለአርሶአደሩ እና ለሀገር ውስጥ የኢንዱስትሪ ፍጆታ እቃዎች አምራቹ የገበያ እድል መፍጠሩ & ከአዲስ አበባ ንግድና ኢንዱስትሪ ቢሮዎች ጋር በመቀናጀት መንግስት በድጎማ ለገበያ ማረጋጊያ የሚያቀርባቸውን የምግብ ዘይት እና ስኳር የሀገር ውስጥና የውጭ ስንዴ በተመደበለት ኮታ መሰረት ለህብረተሰቡ በሸማች ህብረት ስራ ማህበራት በማቅረብ ገበያን ለማረጋጋት ያደረገው ጥረት በተመሳሳይ በአቅርቦት እጥረት ምክንያት የተከሰተውን የሲሚንቶ ዋጋ ውድነት ለማረጋጋት በተመጣጣኝ ዋጋ ለህብረተሰቡ በመሸጥ አጋርነቱን ማሳየቱ የኮርፖሬሽኑ አመራር እና ሰራተኞች ለደንበኞች የሚሰጡት መስተንግዶ ጥሩ መሆኑ በጥንካሬነት ተገልጾል፡፡
እንደ ችግር ከተነሱት ጉዳዮች መካከል በስንዴ፣ የምግብ ዘይትና ስኳር የአቅርቦት መዘግየት መታየት፣ የሲሚንቶ አቅርቦት እጥረት፣ የፍጆታ ምርቶች ግብይት ላይ አስገዳጅ ምርቶችን ውሰዱ መባል የሚሉትን ጉዳዮችን ኮርፖሬሽኑ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመነጋገር መፍትሄ እንዲፈለግ ተሳታፊዎቹ ጠይቀዋል፡፡
ለተነሱት አስተየየቶች የኮርፖሬሽኑ የሥራ ኃላፊዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡ ኮርፖሬሽኑ ደንበኞቹና ባለድርሻ አካላት በሚጠብቁበት ደረጃ አገልግሎቱን ለመስጠት እና ባቀደው ዕቅድ ልክ አፈጻጸሙን ለማሳካት በሀገር ውስጥ በሚፈለገው መጠንና ዋጋ የእህል ምርት ገበያው ላይ አለመገኘት፣ በመንግሥት ድጎማ ለገበያ ማረጋጊያ ከውጭ ሀገር የሚገዛውና በኮርፖሬሽኑ የሚሰራጨው የውጭ ስንዴ ግዥ ጨረታ መስተጓጎል፣ ለገበያ ማረጋጊያ ከውጭ ለሚገዙ የፍጆታ ሸቀጥ ምርቶችም በውጭ ምንዛሪ እጥረት ፍላጎትና አቅርቦቱ አለመመጣጠን፣ ኮርፖሬሽኑ ለውጭ ገበያ የሚያቀርባቸው የቡና፣ የቅባት እህልና ጥራጥሬ ዋጋ በዓለም አቀፍ ደረጃ ካለው የገበያ ዋጋ መብለጥና የምርቶቹ ዋጋ መዋዠቅ ዋነኛ ችግሮች መሆናቸው በውይይቱ ወቅት ተብራርቷል፡፡ ኮርፖሬሽኑ የመንግስት የልማት ድርጅት እንደመሆኑ ወጪውን ራሱ እንደሚሸፍንና የትርፍ ህዳጉ ግን እጅግ ዝቅተኛ መሆኑ ተመላከቷል፡፡
የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ አቻ ደምሴ በውይይቱ ማጠቃለያ በመድረኩ የተሳተፉ አካላትን በማመስገን የተሰጡ አስተያየቶችን እንደ ግብአት ወስደን አገልግሎታችንን ይበልጥ ለማሻሻል እንጠቀምበታለን ብለዋል፡፡ መድረኩ በቀጣይም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ጠቁመዋል፡፡
በመጨረሻም የላቀ አጋርነት ላሳዩ ደንበኞች የእውቅና አሰጣጥ መርሃ ግብር የተካሄደ ሲሆን 13 ደንበኞች የእውቅና የምስክር ወረቀትና የዋንጫ ሽልማት ከኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ አቻ ደምሴ እጅ ተበርክቶላቸዋል፡፡
በሥራ አካባቢ ደኅንነትና ጤንነት ላይ ያተኮረ የሁለት ቀናት ሥልጠና ከኮርፖሬሽኑ ዋና መሥሪያ ቤትና ከንግድ ሥራ ዘርፎች ለተውጣጡና በተለያዩ መደቦች ላይ ለሚሠሩ የሥራ መሪዎችና ሠራተኞች ከግንቦት 9-12/2014 ዓ/ም በሁለት ዙር በዋናው መሥሪያ ቤት የሥልጠና አዳራሽ እየተሰጠ ይገኛል፡፡
ኮርፖሬሽኑ በስፋት እያካሄደ የሚገኘው የአቅም ግንባታ እንቅስቃሴ አንድ አካል የሆነውና ከሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ጋር በመተባበር እየተሰጠ የሚገኘው ይህ ሥልጠና በሥራ አካባቢ ደኅንነትና ጤንነት ዙሪያ የሠራተኛውን ዕውቀትና ክህሎት በማጎልበት ኮርፖሬሽኑና ሠራተኛውን ለአደጋ ሊያጋልጡ የሚችሉ ችግሮችን አስቀድሞ በመተንበይና ተመጣጣኝ የመፍትሔ አማራጮችን በማስቀመጥ ተቋሙ ዓላማዎቹንና ግቦቹን እንዲያሳካ የራሱን አስተዋጽዖ እንደሚያበረክት ተገልጿል፡፡
ሥልጠናው በዋነኝነት በመሠረታዊ የደህንነትና ጤንነት መሠረታዊ ሃሳቦች፣ በሥራ ቦታ ስጋት ግምገማና መቆጣጠሪያ ዘዴዎች፣ በሥራ አካባቢ የደኅንነት ጠንቆችና የመከላከያና መቆጣጠሪያ መንግዶች ላይ ያተኮረ ሲሆን፤ ተሣታፊዎች በሥልጠናው ያገኙትን ክህሎትና ግንዛቤ ወደ ተግባር በመቀየር ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያስችል፣ በሥርዓት የሚመራና በቅንጅት የሚፈጸም የልማት እንቅስቃሴ እንዲኖር ለማድረግ የራሱ አስተዋጽዖ እንደሚኖረው ተገልጿል፡፡ |
የኢትዮጵያ የንግድ ሥራዎች ኮርፖሬሽን በከፍተኛ ሁኔታ የናረውን የዘይት ዋጋ ለማረጋጋት ተጨማሪ የ 10 ሚሊየን ሊትር ፓልም የምግብ ዘይት ግዥ ለመፈጸም ውል ገብቷል፡፡ በቅርቡም ወደ ሀገር ውስጥ እንደሚገባና እንደሚሰራጭ ተገልጿል፡፡ ኮርፖሬሽኑ 12.5 ሚሊየን ፓልም የምግብ ዘይት ከውጭ ወደ ሃገር ውስጥ በማስገባት በአዲስ አበባ እና በሁሉም ክልሎች ባሉ የግብይት ማዕከላት እስከ ሚያዝያ ወር 2014 ዓ/ም መጀመሪያ ሳምንት ድረስ ማሰራጨቱ ይታወሳል፡፡ |
በኮርፖሬሽኑ ዋና መስሪያ ቤትና በአራቱም ዘርፎች የካይዘን እጩ አማካሪዎች የትግበራ ግምገማ ግንቦት 9/2014 ዓ.ም ተካሄደ፡፡ የግምገማ መድረኩን የመሩት አቶ ትእዛዙ ኃ/ ጊዮርጊስ የኮርፖሬት አሰራር ዘዴና የአገልግሎት ማሻሻያ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር እና አቶ አወል ካሳው በካይዘን ኢንስቲቲዩት የሎጀስቲክስ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ናቸው፡፡
የካይዘን ትግበራ በአራቱም ዘርፎችና በዋና መ/ቤት ያለበትን ደረጃ አስመልክቶ የሚመለከታቸው ባለሙያዎች (ፎካል ፐርሰንስ) ገለጻ አድርገዋል፡፡ በአትክልትና ፍራፍሬ ንግድ ስራ ዘርፍ ከካይዘን ትግበራ ጋር በተያያዘ ሁለት ፕሮጀክቶችን (የብልሽት ቅነሳ ስትራቴጂ እና የስራ አካባቢን ምቹ ማድረግ) እየተገበሩ መሆኑ ተመልክቷል፡፡ ለብልሽት ቅነሳ የሚሆኑ መፍትሄዎችን በመለየት ወደ ስራ መግባታቸውን የካይዘን ተጠሪ (ፎካል ፐርሰን) የሆኑት አቶ ዘካሪያስ ተናግረዋል፡፡ አያይዘውም በስራ ግቢ ውስጥ ወድቀው የተገኙ የተለያዩ ማቴሪያሎች ወደ አንድ ቦታ በማከማቸት የተገኘውን ክፍት ቦታ መጋዘን እንዲሰራበት መደረጉን እንዲሁም ንብረት በማስወገድ 900ሺ ብር ገቢ ማግኘታቸውን ገልጸዋል፡፡
በእህልና ቡና ንግድ ስራ ዘርፍ በተመሳሳይ የካይዘን ትግበራው በጥሩ ሁኔታ ላይ እንደሆነ የተገለጸ ሲሆን ለእህል ማደራጃና ማከማቻ ሰራተኞች ስልጠና መሰጠቱ ተጠቁሟል፡፡ ንብረት በማስወገድ ገቢ ማግኘታቸው ተገልጿል፡፡ በዋና መ/ቤት ደግሞ ከማዕድን ሚኒስቴርና ከኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ስራዎች ኮርፖሬሽን የልምድ ልውውጥ መደረጉና ጠቃሚ ተሞክሮዎች መገኘታቸውና መቀመራቸው ተጠቅሷል፡፡ በተመሳሳይ በሌሎችም ዘርፎች ከካይዘን ትግበራ አኳያ የተሰሩ ስራዎችና የተገኙ ገቢዎች በዝርዝር ቀርበው ውይይት ተካሂዶባቸዋል፡፡
አመራሩ የካይዘን ትግበራን ለመተግበርና ለመደገፍ ቁርጠኛ መሆኑ እና ካይዘንን ለመተግበር ምንም ኣይነት የበጀት ችግር አለመኖሩ በጥንካሬ፤ ወጥ የግንኙነትና የውይይት ጊዜ አለመኖር እና በሙሉ አቅም አለመስራት እንደ ክፍተት ከተነሱት ዋንኞቹ ናቸው፡፡ በተነሱ ጉዳዮች ላይ አስተያየትና ማብራሪያ የተሰጠ ሲሆን ቀጣይ የስራ አቅጣጫዎችም ተቀምጠዋል፡፡ በተለይም የድጋፍና ክትትል አግባቡ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ተመልክቷል፡፡
የኢትዮጵያ የንግድ ሥራዎች ኮርፖሬሽን በመንግሥት ድጎማ ከውጭ ለማስገባት በዕቅድ ከያዘው 12.5 ሚሊየን ሊትር ፓልም የምግብ ዘይት ውስጥ መጋቢት 21 ቀን 2014 ዓ/ም የገባውን 2.4 ሚሊየን ሊትር ዘይት ጨምሮ በሦስት ዙር 7.2 ሚሊየን ሊትር ወደ ሃገር ውስጥ ገብቶ ለህብረተሰቡ በማሰራጨት ላይ ይገኛል፡፡ በጅቡቲ ወደብ ላይ የደረሰው 5.3 ሚሊየን ሊትር ዘይት በሁለት ዙር በቅርቡ ወደ ሃገር ውስጥ ይገባል፡፡
ፓልም የምግብ ዘይቱ ባለ ሶስት፣ አምስትና ሃያ ሊትር ሲሆን የምግብ ዘይቱን ተረክበው ለህብረተሰቡ ለማሰራጨት መጋቢት 21 ቀን 2014 ዓ/ም በቃሊቲ የፍጆታ ዕቃዎች ማከፋፈያ መደብር የተገኙ የሸማቾች ህብረት ሥራ ማህበራት ፓልም የምግብ ዘይት በተመደበላቸው ኮታ መሰረት ተረክበዋል፡፡
አቶ ተውፊቅ ይመር የፍጆታ ዕቃዎች ንግድ ሥራ ዘርፍ ሥራ አስፈጻሚ እንደገለጹት የምግብ ዘይቱ በትክክል ለህብረተሰቡ እንዲደርስ ልዩ ክትትል ያስፈልጋል፡፡ ተገዝቶ መቅረቡ ብቻ በቂ አይደለም ያሉት ኃላፊው ሥርጭቱን በአግባቡ ለማከናወን ኮርፖሬሽኑ ሙያው በሚጠይቀው ሥነ-ምግባር መሰረት እየሠራ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡