Algeria01 01.jpg
 
የኢትዮጵያ ንግድ ሥራዎች ኮርፖሬሽን በአልጄሪያ በተካሄደው 52ኛው ዓለም አቀፍ የንግድ ትርዒት ላይ ተሣትፏል፡፡ ከሰኔ 15-20/2011 ዓ/ም በአልጄሪያ ዋና ከተማ አልጀርስ በተካሄደው በዚሁ የንግድ ዓውደ ርዕይ ላይ የኮርፖሬሽኑ የእህልና ቡና ንግድ ሥራ ዘርፍ በአዲስ አበባ የንግድ ምክር ቤት አስተባባሪነት ከሦስት የግል ቡና አምራች ድርጅቶች እንዲሁም ቆዳ አምራቾች ጋር በመሆን የመጀመሪያውን ተሣትፎ አድርጓል፡፡ በትርዒቱ ላይ የኢትዮጵያን የቡና መገኛነት፣ አገሪቱ የምትታወቅበትን የኮፊ አራቢካ የቡና ዙርያ ተመራጭነትና ባህሪ ለተሣታፊዎች ማስተዋወቅ የተቻለ ሲሆን፤ አገሪቱ በዓለም ዓቀፉ የቡና ምርት ግብይት ውስጥ የሚኖራትና ተሣትፎና ድርሻ በተለይም የደንበኞችን ቁጥር ለመጨመርና የኮርፖሬሽኑን ምርቶች ለማስተዋወቅ የሚያስችሉ ግንኙነቶችና ውይይቶች ተደርገዋል፡፡ 
 
አልጄሪያ በዓለም ላይ ቡና ተጠቃሚ ከሆኑ አገሮች አንዷ ሰትሆን በያዝነው የፈረንጆች ዓመት 76 ሺህ ሜትሪክ ቶን ቡና ከውጭ አስገብታለች፡፡ ይሁን እንጂ በዓለም ላይ በጣዕሙም ሆነ በጥራቱ ተመራጭ የሆነ ቡና ለዓለም ገበያ በማቅረብ የምትታወቀው አገራችን ከዚህ ገቢ ምርት ውስጥ የነበራት ድርሻ 19 ሜትሪክ ቶን ወይም ከ1 በመቶ ያነሰ ሆኖ መገኘቱ በቡና ወጪ ንግድ ላይ ድርሻን ተሣትፎን እጅጉን ማጎልበት እንደሚያስፈልግ አመላክቷል፡፡
 
በአሁኑ ወቅት በቡና ወጪ ንግድ ዘርፍ የሚታዩ ተግዳሮቶች እየጠነከሩ ከመምጣታቸው ጋር ተያይዘው የሚፈጠሩ ቀስ በቀስ ከገበያ የመውጣት ስጋቶችን ከወዲሁ ማስቀረት ከመቻል አኳያ በንግድ ትርዒቱ ላይ ከተደረገው ተሣትፎ የተወሰዱ ግንዛቤዎች አዎንታዊ ሚና እንደነበራቸው ተገልጿል፡፡ 
 
አልጄሪያ በሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ድጋፍ ሰጪነት በተዘጋጀ መድረክ ከተለያዩ ዓለም አቀፍ ባለድርሻ አካላት በተለይም ከቡና አስመጪዎችና ኢንቬስተሮች ጋር መገናኘትና በተለያዩ የንግድ ማሻሻያ ጉዳዮች ላይ ገንቢ ውይይት ማድረግ መቻሉ ተገልጿል፡፡ ለአብነትም በአልጄሪያ የብራዚል አምባሳደርን ጨምሮ ከሌሎች አገሪቱን ወክለው በንግድ ትርዒቱ ላይ የተገኙ ተሣታፊዎች የአገራችን የቡና ምርት የጎበኙ ሲሆን በተመሳሳይም ኢትዮጵያን ወክለው የተሣተፉ ባለሙያዎች የብራዚል ምርቶችን በመጎብኘት ጠቃሚ ግንዛቤዎችን መወሰድ ችለዋል፡፡ 
 
 
ኢትዮጵያ ለዓለም ገበያ ማቅረብ የምትችለው ቡና በጥራቱ ከፍተኛና ተፈላጊ ሆኖ ሳለ ሌሎች አምራች አገራት ከዚህ ያነሰ ጥራት ያለው ምርት ይዘው የተሻለ ገበያ ማግኘት መቻላቸው አገሪቱ በንግዱ ዘርፍ ልትፈታቸው የሚገቡ ጉልህ ክፍተቶች መኖራቸውን ከዓውደ ርዕዩ  ተሣትፎ መረዳት ተችሏል፡፡ በተለይም በአገር ውስጥ የሚቀርበው የቡና ምርት የመግዣ ዋጋ ከዓለም የገበያ ዋጋ በእጥፍ ከሚልቅ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ ኤክስፖርተሮች ከዓለም ገበያ ውጭ መሆናቸው፤ የቡና ምርት ከአገር ውስጥ ገበያ ከተገዛበት በታች በሆነ ዋጋ ሲሸጥ በሚመለከተው አካል እርምጃ አለመወሰዱ ወይም የወጪ ንግድ የዋጋ ወለል መሰን አለመቻሉ በዓለም አቀፉ ገበያ ላይ በሚፈለገው ልክ ተወዳዳሪ ሆኖ ላለመውጣት ምክንያት መሆናቸው ተጠቅሷል፡፡ 
 
በአልጄሪያ ከሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ አማካኝነት ከአልጀሪያ ቻምበር ኦፍ ኮሜርስ ጋር በመተባበር ከንግዱ ማህበረሰብ ጋር ጠቃሚ የB to B የንግድ ውይይት በጥልቀትና በተናጥል በማድረግ በቀጣይ ከኮርፖሬሽኑ ጋር የሥራ ግንኙነት ለመጀመር ከሚችሉ ደንበኞች ጋር ውይይት ተደርጓል፡፡ በኢትዮጵያ ኤምባሲ አማካኝነት ንግድ ትርዒቱ ላይ ለመሳተፍ ከመጡ የብራዚል ኤክስፖርተሮች ጋር በአምባሳደራቸው በኩል የልምድ ልውውጥ ለማድረግ ተችሏል፡፡ 
 
በሌላ በኩል ጥራጥሬ ፣ ቅባት እህል፣ ቅመማ ቅመም እና ቡና ኢምፖርት ለማድረግ የሚፈልጉ አስመጪዎች ፍላጎታቸውን የገለፁ ሲሆን፤ ነገር ግን የአገሪቱ የአቅርቦት ዋጋ ከፍ ያለ በመሆኑ በወቅቱ ካለው ዓለም አቀፍ ዋጋ አንፃር እጅግ ውድና አዋጪ አለመሆኑን በመግለፅ ስምምነት ላይ ለመድረስና ውል ለመዋዋል ሳይቻል ቢቀርም ቀጣይ ግንኙነቶችን በማድረግ የንግድ ግንኙነቶችን ለማሳካት ጥረት የሚደረግ መሆኑ ተገልጿል፡፡
 
እነዚህ ችግሮች መፈታት ከቻሉ ኮርፖሬሽኑ የንግድ ዘርፉን ለማጎልበት ካለው አቅም ጋር ተዳምሮ በቀጣይ የቡና ምርት ግብይትን ማጎልበት የሚቻል መሆኑን ለመገንዘብ ተችሏል፡፡ በተለይም የቡና ምርትን በፍሬ ደረጃ ለገበያ ከማቅረብ ባሻገር የአገሪቱን የተለያዩ የቡና ዝርያዎች የዓለም አቀፉ ገበያ በሚፈልገው ዓይነት በፋብሪካ አቀነባብሮ እሴትን በመጨመር በቀጥታ ለተጠቃሚዎች ፍጆታ ማቅረብ መቻል በዘርፉ በተሻለ ተወዳዳሪ ለመሆን እንደሚረዳ ከዓውደ ርዕዩ  ተሞክሮ መገንዘብ ተችሏል፡፡ በተጨማሪም ኮርፖሬሽኑ በዘርፉ የሚታዩ የገበያና የግብይት ችግሮችን ከባለድርሻ አጋራት ጋር በመሆን ለመፍታት በመንቀሳቀስ የንግድ ዘርፉን ለማሳደግ የበኩሉን ድርሻ ለመወጣት ዝግጁ መሆኑ ተመልክቷል፡፡
 
በዓውደ ርዕዩ ላይ ፈረንሣይ፣ ስፔይን፣ ብራዚል፣ የመካከለኛው ምስራቅ አገራት፣ ካናዳ፣ ማሊ፣ ሴኔጋልና ሌሎችም በቡና ምርትና ንግድ ግንባር ቀደም ሥፍራን የያዙ አገራትና ኩባንያዎች ተሣትፈዋል፡፡
Algeria02 02.jpgAlgeria03 03.jpg
addis.jpg
አዲስ አበባችን ለረጅም አመታት በመዝናኛ ቦታዎች እጥረት ነዋሪዎቿ ሲወቅሷት ኖረዋል:: ከተሞች የቱንም ያህል በመሰረተ ልማት ቢለሙም በወንዝ ዳርቻዎች የሚካሄድ ልማት ከሚሰጠው የአእምሮ እርካታ አንጻር እምብዛም ነው፡፡ በእኛም ሀገር ሁኔታ በወንዞችና ሀይቆች ዙሪያ የተመሰረቱ ከተሞች ምን ያክል ነዋሪዎቻቸውን አለፍ ሲልም ከሌላ አካባቢ የሚመጡ ጎብኝዎችን አእምሮ እንደሚያዝናኑ ግልጽ ነው፡፡ መዲናችን አዲስ አበባ ጸጋው እያላት ጸጋዋን ሳታለማና ሳትጠቀምበት ለረጅም ግዜ ቆይታለች፡፡ አሁን ግን ለረጅም ጊዜ የቆሻሻ መጣያ ሆነው የከረሙ ወንዞቿን ለማልማት ቆርጣ ተነስታለች፡፡
ከእንጦጦ ተራራ እስከ አቃቂ ከተማዋን ለሁለት ከፍለው በሚፈሱ ወንዞች ግራና ቀኝ የሚሰራው የወንዝ ዳርቻ ልማት የተግባር እንቅስቃሴ ተጀምሯል፡፡ ልማቱ 51 ኪ/ሜ ርዝመት የሚሸፍን ሲሆን በ29 ቢሊዮን ብር ወጭ ይከናወናል፡፡ የወንዝ ዳርቻው ልማት ለበርካታ ዜጎች የስራ እድል ከመፍጠሩም በላይ ከተማዋን ጽዱና ማራኪ በማድረግ በኩል ድርሻው የጎላ ነው፡፡ የወንዝ  ዳርቻ ልማቱ ሲጠናቀቅ መዲናችንን እንደ ስሟ አዲስ አበባ ውብ እና ማራኪ በማድረግ የቱሪዝም መስኩን የበለጠ በማነቃቃት በኩል ልዩ ትርጉም ይኖረዋል፡፡ ይህ ፕሮጀክት ሲጠናቀቅ በሳምንቱ መጨረሻ በስራ ደክሞ የሰነበተ አእምሯቸውን ዘና ለማድረግ ከአዲስ አበባ ውጭ ለሚጓዙ የከተማዋ ነዋሪዎች መልካም አጋጣሚ ይሆንላቸዋል፡፡ በዚህም ጊዜያቸውንና ገንዘባቸውን እንዲሁም ድካማቸውን መቀነስ ያስችላቸዋል፡፡  ከዚህም በተጨማሪ በየእለቱ በትርፍ ሰዓታቸው መዝናናት ለሚፈልጉ የመዲናዋ ነዋሪዎች እንደ መዝናኛ አማራጭ ከመሆኑም ባሻገር ከተማዋን ጽዱና ማራኪ በማድረግ በኩል ድርሻው የጎላ ነው፡፡ 
የኢትዮጵያ ንግድ ሥራዎች ኮርፖሬሽን በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ በሚያደርጋቸው ተሳትፎዎች የዳበረ ልምድ ባለቤት ነው፡፡ በማህበራዊ ጉዳዮች በመሳተፍና ድጋፍ በማድረግ በጎ አድራጎት ተግባራት ላይ ግንባር ቀደም ተሳትፎ ያለው ኮርፖሬሽኑ በ “ሸገርን ማስዋብ” እቅድ ላይም ያሳየው ይህንኑ ነው፡፡ በአሁኑ ጊዜ ይህ የወንዝ ዳርቻ ልማት ከግብ እንዲደርስ ባለድርሻ አካላት ርብርብ በማድረግ ላይ ሲሆኑ የኢትዮጵያ ንግድ ስራዎች ኮርፖሬሽን 250¸000 ብር ድጋፍ ለማድረግ ቃል የገባ ሲሆን በቀጣይም አጋርነቱን ለማረጋገጥ ቁርጠኛ መሆኑ ታውቋል፡፡ በእርግጥም ሸገርን ማስዋብ ትኩረት ሊነፈገው የማይገባው ጉዳይ መሆኑ ለሁላችንም ግልጽ ነው፡፡

ከግንቦት 1-5/2011 ዓ.ም በአዲስ አበባ በተካሔደው 12ኛው አዲስ ቻምበር የእርሻና ምግብ አለም አቀፍ ንግድ ትርኢት ከተለያዩ ዘርፎች ልዩልዩ ምርቶችን በማስተዋወቅ ለተከታታይ 5 ቀናት በተካሔደው ንግድ ትርኢት ላይ የኢትጵያ ንግድ ሥራዎች ኮርፖሬሽን ተሳትፏል፡፡

ይህም የኮርፖሬሽኑ ዘርፎች ለሚያቀርቡት ምርትና አገልግሎት ከደንበኞች እና ከአቅራቢዎች ጋር ለመገናኘት መልካም አጋጣሚ ነው፡፡የውጭና የአገር ዉስጥ ደንበኞችን አመለካከት በማሻሻል ረገድም ንግድ ትርኢቱ ሚናው የጎላ መሆኑ ታምኖበታል፡ ከሁሉም በላይ ግን ኮርፖሬሽኑ በህዝብ ዘንድ እውቅና እንዲፈጠርለት ከማድረግ አኳያ ንግድ ትርኢቱ ተኪ የሌለው ሚና ይጫወታል፡፡

በንግድ ትርኢቱ ከእህልና ቡና ንግድ ሥራ ዘርፍ፣ ከፍጆታ እቃዎች ንግድ ሥራ ዘርፍ እና ከአትክልትና ፍራፍሬ ንግድ ሥራ ዘርፍ የተለያዩ ምርቶችንና አገልግሎቶችን ለህዝብ የማስተዋወቅ ሥራ ተሰርቷል፡፡

በዚሁ   መሠረት ከተለያዩ የውጭ አቅራቢ ድርጅቶች ጋር ቀጣይ ግንኙነቶችን ማድረግ የሚቻልባቸው ሁኔታዎች ላይ ውይይት ተደርጓል፡፡ እነዚህ አቅራቢ ድርጅቶችም ኢትዮ-አግሮ ሴፍቲ ኃ/የተ/የግ/ማ የሻይ ምርት ማዘጋጃና ማቀነባበሪያ ፋብሪካ፣ ሊዩስ የምግብ ዘይትና አኩሪ አተር ምርቶች፣ ጭላሎ ምግብ ኮምፕሌክስ ሲሆኑ በቀጣይ አብሮ ለመሥራት የሚያስችል ቅድመ ትውውቅ ሥራ ተሠርቷል፡፡

የኢትዮጵያ ንግድ ሥራዎች ኮርፖሬሽን ከሚያዚያ4-7/2011 ዓ/ም በባህር ዳር ከተማ በተካሄደው 1ኛው አለም አቀፍ ኢንቨስትመንት ፎረም እና የንግድ ትርዒት ባዛር ተሳትፎው በሁሉም ንግድ ሥራ ዘርፎች የሚቀርቡ ምርትና አገልግሎቶችን ለጎብኝዎች ማቅረብ ተችሏል፡፡ አንድ የንግድ ተቋምን ለማሳደግና በተሻለ ሁኔታ ቢዝነሱን ለማከናወን እንዲችል የገበያ ልማት ሥራ መሥራት በጣም ወሳኝ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ስለሆነም የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ስለኮርፖሬሽኑ ጠቃሚ መረጃ እንዲያገኙ ተደርጓል፡፡ 

ለሸማች ማህበራት፣ ለአርሶ አደሮች፣ ለጅምላ አከፋፋዮች፣ ለቸርቻሪዎች፣ ለኢንቬስተሮችና ለውጭ ሃገር ተሳታፊዎች ኮርፖሬሽኑን ማስተዋወቅ ተችሏል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በንግድ ትርዒቱ በኮርፖሬሽኑ በተዘጋጀው የቡና ጠጡ ፕሮግራም ላይ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን በመጋበዝ ኮርፖሬሽኑ ስለተቋቋመበት አላማና በኮርፖሬሽኑ ስለሚቀርቡ ምርትና አገልግሎቶች ዝርዝር ማብራሪያ ተሰጥቷል፡፡

የተለያዩ የሚዲያ አካላት ስለኮርፖሬሽኑ ዝርዝር መረጃ በአካል ተገኝተው በመጎብኘትና ሰራተኞችን ቃለ-መጠይቅ በማድረግ ልዩ ትኩረት ሰጥተውታል፡፡ የጎብኚዎችን ግብረ መልስ በተመለከተ በተለይ የፍጆታ እቃዎች ለምሳሌ ከውጪ የሚገቡ የዘይት ምርቶች በንግድ ትርዒቶች ላይ ለሽያጭ የሚቀርቡበት ዕድል ቢኖር፤ በፍጆታ እቃዎች ንግድ ሥራ ዘርፍ የሚሠጠው አገልግሎት ለተቋማትና ቲን ቁጥር/ፈቃድ ላላቸው ብቻ የሚከናወን በመሆኑ ሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ የማያደርግ ስለሆነ ይህ አሰራር ቢቀየር፤ እንዲሁም በአትክልትና ፍራፍሬ ንግድ ሥራ ዘርፍ በኩል የሚሸጡ ምርቶች የሚሸጡበት ዋጋ ዙሪያ ማስተካከያ ቢደረግ የሚሉ አስተያየቶችና ግብረ መልሶች ተወስደዋል፡፡

የኢትዮጵያ የንግድ ሥራዎች ኮርፖሬሽን የ2011 ዓ/ም በጀት ዓመት የ9 ወራት እቅድ አፈጻጸም የኮርፖሬሽኑ ከፍተኛ አመራሮች፣ ዳይሬክተሮች፣ የቡድን መሪዎችና ከፍተኛ ባለሙያዎች በተገኙበት ተካሂዷል፡፡ በግምገማው የኮርፖሬሽኑ የእህልና ቡና፣ የፍጆታ ዕቃዎች፣ የአትክልትና ፍራፍሬ እንዲሁም የግዥና ማማከር አገልግሎት የንግድ ሥራ ዘርፎች ዕቅድ ክንውናቸውን ቀርቦ ውይይት ተደርጓል፡፡

በእህልና ቡና ንግድ ሥራ ዘርፍ በ2011 በጀት ዓመት ዘጠኝ ወራት ከተለያዩ የሃገር ውስጥ የግዥ ምንጮች 937,034 ኩንታል የብዕር እና የአገዳ እህል፣ ጥራጥሬና ቡና ለመግዛት ታቅዶ 785,481 ኩንታል ግዥ የተከናወነ ሲሆን አፈጻጸሙም 84% ነው፡፡ ሌሎች እህሎች ከመግዣ ዋጋ ንረት ጋር በተያያዘ ግዥ አልተፈጸመም፡፡ ኮርፖሬሽኑ በእህልና ቡና ንግድ ሥራ ዘርፍ በኩል ገበያን ለማረጋጋት ተግባር 1.151 ሚሊዮን ኩንታል ከሀገር ውስጥ ገበያ የስንዴ ግዢ ለማከናወን በ2011 በጀት ዓመት ዘጠኝ ወራት ዕቅድ የተያዘ ቢሆንም በዋጋ መናር ምክንያት በመንግስት እንዳይገዛ በመወሰኑ ግዥ እንዳልተከናወነ በአፈጻጸም ግምገማ ተመላክቷል፡፡

ኮርፖሬሽኑ በሃገር ውስጥና በኤክስፖርት ሽያጭ በ2011 በጀት ዓመት ዘጠኝ ወራት ውስጥ የገበያ ማረጋጋት ሥራን ጨምሮ በሀገር ውስጥና በውጭ ገበያ 5.95 ሚልዮን ኩንታል እህልና ቡና ለመሸጥ አቅዶ 4.25ሚልዮን ኩንታል እህልና ቡና በመሸጥ የዕቅዱን 71 በመቶ መከናወኑ በሪፖርቱ ላይ ተመልክቷል፡፡ 

በዘጠኝ ወራቱ በወጪ ንግድ 70,500 ኩንታል የታጠበ እና ያልታጠበ ቡና ለመሸጥ አቅዶ 29,760 ኩንታል ቡና ለተለያዩ ሀገሮችና ደንበኞች በመሸጥ የዕቅዱ 42 በመቶ የተከናወነ ሲሆን በዘጠኝ ወራት ውስጥ 8,458,602.59 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር ከቡና ኤክስፖርት ገቢ መገኘቱ ተገልጿል፡፡ ሆኖም ግን ከ2010 በጀት አመት ተመሳሳይ ወቅት አፈጻጸም ጋር ሲነጻጸር የ24% ቅናሽ አሳይቷል፡፡

በአትክልትና ፍራፍሬ ንግድ ሥራ ዘርፍ 231,071 ኩንታል ፍራፍሬ፣ አትክልት፣ የአትክልት ዘር፣ የፋብሪካ ምርት፣ ስኳር፣ የሃገር ውስጥ ዘይት፣ ፓልም ዘይትና ሌሎች ለመግዛት ታቅዶ 155,323 ኩንታል (የዕቅዱ 67%) መከናወኑ ተገልጿል፡፡ የግዢ አፈጻጸሙ ከ2010 በጀት አመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ28% ቅናሽ ያሳየ ሲን ለዚህም በምክንየትነት የተቀመጡት ጉዳዮች መካከል ዋና የፍራፍሬ አቅራቢ ከሆነው ከላይኛው አዋሽ አግሮ ኢንዱስትሪ የሚነሳው የብርቱካን ምርት መቀነስና በበጀት ዓመቱ ከአምስት ያላነሱ ነጋዴዎች ወደ ግብይቱ በመግባት ምርቱን ማንሳት በመጀመራቸው የአቅርቦቱ ማነስ መሆናቸው ተጠቅሷል፡፡ ዘርፉ በበጀት ዓመቱ በሃገር ውስጥ ሽያጭ 227,057 ኩንታል ተመሳሳይ ምርቶችን ለመሸጥ ታቅዶ 152,692 የተከናወነ ሲሆን ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት አፈጻጸም ጋር ሲነጻጸር በመጠን 23% ቅናሽ አሳይቷል፡፡ በአንጻሩ በውጭ ሀገር ገበያ 9,173 ኩንታል ፍራፍሬ ለመሸጥ ታቅዶ የ4,575 ኩንታል ሽያጭ ማከናወን መቻሉ ተገልጿል፡፡ 

በዘርፉ እየተከናወኑ ያሉ ፕሮጀክቶች ያሉበት የሥራ ደረጃ በተመለከተ የአትክልት ምርቶች በኮንትራት ለማስመረት ከጂቱ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ጋር የአትክልት ምርቶችን በኮንትራት ለማስመረት ውል መፈረሙና ሲሆን ከሰኔ ወር 2011 ዓ/ም ጀምሮ ለገበያ የማቅረብ ሥራ ይጀመራል ተብሎ እንደሚጠበቅ በሪፖርቱ ተመልክቷል፡፡ 

በሌላ በኩል የፍጆታ ዕቃዎች ንግድ ሥራ ዘርፍ በበጀት ዓመቱ 637,336 ኩንታል የተለያዩ የፍጆታ ዕቃወችን ለመግዛት አቅዶ 358,701 ኩንታል ማከናወኑና የግዥ አፈጻጸሙ ከ2010 በጀት ተመሳሳይ ወቅት አፈጻጸም ጋር ሲነጻጸር የ29% በመቶ ቅናሽ ማሳየቱ ተጠቅሷል፡፡

የግዥ ሥራዎችን እና አቅርቦት በተመለከተ በዘጠኝ ወራቱ አዳዲስ 46 በምርትና በአይነት የተለያዩ ምርቶች ከሀገር ውስጥ ተገዝተው መቅረባቸው የተገለጸ ሲሆን በአዲስ ከቀረቡት ውስጥ 26 ዓይነት ምርቶች ቀድመው ይቀርቡ የነበሩ ነገር ተቋርጠው የነበሩና በአዲስ ውልና ድርድር የቀረቡ መሆናቸው ተመልክቷል፡፡ በሌላ በኩል 14 አዳዲስ አምራቾችን ወደ ድርጅቱ ማምጣት መቻሉ የተገለጸ ሲሆን በአጠቃላይ 637,336 ኩንታል ምርት ለመሸጥ ታቅዶ 448,632 መሸጡ ተገልጿል፡፡

በግዥና ማማከር አገልግሎት ዘርፍ በዘጠኝ ወራቱ የ580 ሚሊዮን ብር የአገልግሎት ግዥ የተከናወነ ሲሆን፤ ከዚህ ውስጥ በገቢ ይመዘገባል ተብሎ ከታቀደው ብር 10.59 ሚሊዮን ውስጥ የተከናወነው ብር 8.37 ሚሊዮን መሆኑ ተገልጿል፡፡ በሌላ በኩል በሪፖርት ወራቱ ከምክርና ሥልጠና ገቢ ለማግኘት ታቅዶ ከነበረው ብር 1.3 ሚሊዮን ውስጥ ለተለያዩ 306 መንግሥታዊና መንግሥታዊ ላልሆኑ ድርጅቶች ለተውጣጡ ሠልጣኞች የግዥ ሥልጠና በመስጠት ብር 1.24 ሚሊዮን ገቢ መገኘቱ ተገልጿል፡፡ በአጠቃላይ 12,377,636.32 ብር ገቢ ለማግኘት ታቅዶ 9,693,563.23 መከናወኑ ተመልክቷል፡፡

የኮርፖሬሽኑ የዘጠኝ ወራት አፈጻጸም ግምገማ ተሣታፊዎች በቡድን ባካሄዷቸው የቡድን ውይይቶችና የተገመገሙ ሲሆን  የታዩ ችግሮችና የመፍትሔ ሃሳቦች በስፋት ቀርበዋል፡፡ ከተነሱ አበይት ችግሮች መካከል የውጭ አገር ሽያጭ መቀዛቀዝ፣ በአንዳንድ የግብይት ሰብሎች (ለምሣሌ ኑግ፣ በቆሎ፣ ሽምብራ) የሀገር ውስጥ የመግዣ ዋጋ ከውጭ አገር መሸጫ ዋጋ መብለጥና ከፍተኛ የሆነ የምርት ክምችት መኖር፣ የመግዣና መሸጫ ዋጋ ውሳኔ የተማከለ መሆን እና ፈጣን ምላሽ የሚሰጥበት አካሄድ አለመኖሩ፤ የገበያ ማፈላለግ ሥራ በአንጻራዊነት ደካማ መሆን፤ በኮርፖሬሽኑና በዘርፉ መካከል የሥልጣንና ሀላፊነት ግልጽነት ጉድለት መታየቱ፤ በበሀብት አጠቃቀም እና ንብረት አስተዳደር ላይ ችግር መኖሩ፤ የተሟላ የኢንሹራንስ ሽፋን አለማግኘት፤ በግዥና በሽያጭ ደንበኛን የማፈላለግና የማቆየት ችግር ነባር ደንበኞች ላይ ብቻ ትኩረት ማድረግ የሚሉት ይገኙበታል፡፡ በዘርፉ በመፍትሔ አማራጭነት ከተቀመጡት ሃሳቦች መካከልም እሴት ጨምሮ መሸጥ ላይ የበለጠ ትኩረት ማድረግ፤ የግብይት ሥራዎች በተሻለ ውጤታማ እንዲሆኑ ኮርፖሬሽኑ የገበያ ማፈላለግ ሥራን ከሌሎች አካላት ጋር ተቀናጅቶ መሥራት እንደሚያስፈልገው፤ ሀብትና ንብረቶች ይበልጥ በተደራጀ አኳኋን አግባብነት ያለው ባለቤት ተፈጥሮላቸው እንዲ ተዳደሩ ማድረግ፤ የመጋዘን ጥገና ሥራዎች በወቅቱ ተከናውነው የተሟላ አገልግሎት እንዲሰጡ ማድረግ የሚሉት ይገኙበታል፡፡ 

በተመሣሣይም በአትክልትና ፍራፍሬ የንግድ ሥራ ዘርፍ ክንውን ላይ የተለያዩ ጉዳዮች በተሣታፊዎች የተዳሰሱ ሲሆን፤ የኮንትራት ፋርሚንግ ሥራ ተጠናክሮ አለመቀጠሉ፤  የምርት አቅራቢዎች ቁጥር ውስን መሆኑ፤ የውጭ ምንዛሪ እጥረት፤ በአንዳንድ የሽያጭ ሠራተኞች ላይ የሥነ ምግባር ችግር መታየቱ፤ የምርት ብልሽትን አስቀድሞ የመከላከል ችግር ሙሉ ለሙሉ አለመቀረፉ እንደ ችግር የተነሱ ሲሆን የመሸጫ ሱቆችን ማዘመን፤ የተለያዩ የግንዛቤ ማሳደጊያ ሥራዎችን በማከናወን የአቅራቢዎችን ቁጥር መጨመር፤ አቅም ካላቸው የክልል አምራቾች ጋር የገበያ ትስስር መፍጠር፤ ህገ-ወጥ ንግድን ከሚመለከተው ጋር በመሆን እንዲፈታ ጥረት ማድረግ፤ ከሌሎች ዘርፎች ጋር በተሻለ ተቀናጅቶና ተናብቦ መሥራት በሚሉት ጉዳዮች ላይ ትኩረት ተሰጥቶ መሠራት እንዳለበት ተጠቁሟል፡፡ 

ከፍጆታ ሸቀጦች ንግድ ሥራ ጋር በተያያዘም በተለይም በአለ በጅምላ በብድር የተወሰደው ገንዘብ እንዲመለስ ኮርፖሬሽኑ ከሌሎች ጋር በመተባበር እንዲፈታ ማድረግ እንዲሁም ለፍጆታ አቃዎች በብድር የተሰጠ ገንዘብ እንዲመለስ ማድረግ ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እንዲሠራ ሃሳብ ቀርቧል፡፡ 

በተጓዳኝ የሥራ ሂደቶች ክንውን ዙሪያ በተደረጉ የቡድን ውይይቶች ከተነሱ አንኳር ጉዳዮች መካከል ከጅንአድ የተዛወረ 8000 ካ/ሜ መካዝን ወደ ሥራ እንዲገባ ማድረግ፤ የምርት ሥርጭት /በተለይም ወደ መዳረሻ የሚሄዱ ሸቀጦች/ በተሻለ ጥራት እዲከናወን ማድረግ፤ የሂሳብ ምርመራዎች በወቅቱ እንዲካሄዱ ማድረግ፤ የውጤት ተኮር ሥልጠና በተለይ በሥራ አመራሩ ውስጥ ሊያሰርጽ በሚያስችልበት አኳኋን እንዲካሄድ ማድረግ፤ የለውጥ መሳሪያዎች በአውቶሜሽን እንዲደገፉ ማድረግ፤ የኮርፖሬት አስተሳስብን የመፍጠር ሥራዎች ደካማ በመሆናቸው በቀጣይ በተጠናከረ መልኩ ማከናወን፤ የሕዝብ ግንኙነት ሥራዎችን በተሻለ ጥራትና ወቅታዊነት እንዲከናወኑ ማድረግ፤ ለህግ ከቀረቡ ጉዳዮች መካከል 60 በመቶ በማሸነፍ ቀሪው 40 በመቶ ደግሞ በሽነፈት የተጠናቀቁ ከመሆናቸው ጋር ተያይዞ የሽንፈቶቹ መሠረታዊ ምክንያቶች ተለይተው ተገቢው የማስተካከያ እርምጃ እንዲወሰድ ማድረግ፤ በክርክር ላይ በሽንፈት ምክንያት የሚመጣውን ኪሳራ ለማስቀረት ቅድመ መከላል ላይ ማተኮር፣ የማማከር እንዲሁም ጉዳዮችን በድርድር የመፍታት አቅምን ማዳበር በሚሉት ላይ ትኩረት ተደርጎ መሠራት እንዳለበት ተጠቅሷል፡፡  በመጨረሻም በተነሱ ጉዳዮች ላይ በአመራሩ ሰብሳቢነት አጠቃላይ ውይይት ተደርጎ የግምገማ መድረኩ ተጠናቋል፡፡